Wednesday, January 11, 2017

በባህርዳር ግራንድ ሪዞርትና ስፓ የታሰበው የገና ጨዋታ የበዓል ዋዜማ ኮንሰርት በቦታው በደረሰው የቦንብ ጥቃት ምክንያት ሳይደረግ ቀርቷል

በናትናኤል መኮንን
በባህርዳር ግራንድ ሪዞርትና ስፓ የታሰበው የገና ጨዋታ የበዓል ዋዜማ ኮንሰርት በቦታው በደረሰው የቦንብ ጥቃት ምክንያት ሳይደረግ ቀርቷል። ህወሓት አገዛዝ በነዋሪወች ላይ ካለው ንቀትና አስመሳይ ባህሪው የተነሳ በቁስላችን ላይ እንጨት ለመቀሰር፣ በተቀጣጠለው የህዝብ ቁጣና አመፅ ላይ ውሃ ለመቸለስ ና የስነ ልቦና ጫና ለመፍጠር ያደረገው ጥረት አልተሳካም።
ረዕቡ ምሽት 2 ሰዓት ታህሳስ 26 ቀን የደረሰው የቦንብ የማስጠንቀቂያ ፍንዳታ ምክንያት ያሰበው እንደማይሆን ያወቀውና እንዳቀደው ያልሆነለት ህወሓት/ብአዴን ባለስልጣናት ኮንሰርቱን ወደ አይሲቲ ኢንኩቤሽን ወይም ሙሉዓለም የባህል ማዕከል ጎን ካለው ህንፃ ለማድረግ የተገደዱ ቢሆንም በኮንሰርቱ 120 ትኬቶች ለብአዴን ባለስልጣናት ና ጀሌወቻቸው የተሸጠ ቢሆንም በቦታው የተገኙ ከ50 ያነሱ መሆናቸው ታውቋል። ከፍተኛ የፌደራልና የክልሉ ልዩ ሃይል (የአድማ በታኝ) ወታደሮች ቁጥጥር ሲደረግለት የነበረው ኮንሰርት በባእሉ ዕለት ማግስት ታህሳስ 30 በድጋሚ ህዝብ እንዲገባ ሲለፍፍ የዋለ ቢሆንም ምንም ታዳሚ ሰው አለመገኘቱ ታውቋል። በዚህ ኮንሰርት የኮንሰርቱ አዘጋጆችና የህወሓት/ብአዴን ሹማምንቶች ከፍተኛ ኪሳራ እንዳጋጠማቸው ታውቋል። በኮንሰርቱ ላይ ለመዝፈን የመጡ ድምፃዊያን ታምራት ደስታ፣ ጆኒ ራጋ፣ እሱባለው፣ ያሬድ ነጉ ና ሌሎች መሆናቸው ታውቋል። እነዚህ ድምፃዊያን አርቲስቶች በኮንሰርቱ እንዳይገኙ ተደጋጋሚ የህዝብ ጥያቄ የቀረበላቸው ቢሆኑም በማናለብኝነት በባህርዳር ህዝብ ሊቀልዱ በኮንሰርቱ ላይ መገኘታቸው በቀጣይ ከነፃነት በኋላ የህዝብን ፍርድ ይጠብቁ!! ህዝባዊ አመፅንና ህዝባዊ እምቢተኝነትን በእስር ና በግድያ አፍኖ ለማስቆም የሚታትረው የህወሓት አፍኝ ቡድን የቦንብ ጥቃት በደረሰበት ሰዓት ጀምሮ ከዚህ ቀደሙ በባሰ ሁኔታ በግራንድ ሪዞርት ና ስፓ አካባቢ የተገኙ ባለ ባጃጆችን፣ መንገደኞችን ጨምሮ የሪዞርቱ ሰራተኞችን ያሰረ ሲሆን የወ/ሮ ትልቅ ሰው ገዳሙ ስም ያለው ህንፃ ውስጥ በቦንብ ጥቃቱ ሰዓት ትክክለኛ መጠኑ ያልታወቀ ብር በመጥፋቱ ተጨማሪ ምክንያት ንፁሃን ተረኛ ሰራተኞች ታፍሰው መታሰራቸው ታውቋል።
በባህርዳር ከተማ ከፍተኛ የእስር ና የግድያ ዘመቻ እየተደረገባት ይገኛል።

No comments:

Post a Comment